Monday, December 16, 2013

መድረክ ሠላማዊ ሠልፎች እንዳይካሄድ መከልከሉን አስታወቀ December 14, 2013

የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ፤ ባልወጣ ህግ እና የባቡር ፕሮጀክቱን ሠበብ በማድረግ፣ በአዲስ አበባ ለማካሄድ ያቀዳቸውን ሠላማዊ ሠልፎች እንዳይካሄድ መከልከሉን አስታወቀ፡፡ ፓርቲው፤ የሠላማዊ ተቃውሞን መንገድ መዝጋትና የዜጐችን ህገ-መንግስታዊ መብቶች ማፈን በአስቸኳይ እንዲቆም ጠይቋል፡፡ የመድረኩ አመራሮች በትናንትናው እለት በፓርቲው ፅ/ቤት ለጋዜጠኞች በሠጡት መግለጫ፤ ሐምሌ 7 ቀን 2005 ዓ.ም በኢህአዴግ እየተፈፀሙ ናቸው ያላቸውን ኢ-ሠብአዊና ፀረ ዲሞክራሲያዊ የመብት ጥሠቶችና ህገ-መንግስቱን የሚፃረሩ ህጎችና አዋጆች እንዲሻሻሉ ወይም እንዲቀሩ ለመጠየቅ አዘጋጅቶት የነበረው ሰላማዊ ሰልፍ፣ የባቡር ሃዲድ ስራን በማሳበብ መከልከሉን ገልጿል፡፡
በተመሳሳይ ህዳር 8 ቀን 2006 ዓ.ም በሳውዲ አረቢያ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ የደረሰውን ግፍ ለመቃወም አዘጋጅቶት የነበረው ሰላማዊ ሰልፍም “ፀጥታ የሚያስከብር የፖሊስ ሃይል የለኝም” በሚል ሰበብ በመንግስት እንደተከለከለ መድረኩ ገልጿል፡፡ ለ3ኛ ጊዜ ያዘጋጀውና በአገሪቱ አሳሳቢ ናቸው ያላቸውን ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮችን ለመንግስት ለማሳሰብ፣ ህዳር 29 ቀን 2006 ዓ.ም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ያቀረበው ጥያቄ፣ እውቅና ሰጪው አካል በይፋ ያልወጣና ገና በህትመት ላይ የሆነን ደንብ በመጥቀስ “የጠየቃችሁበት ስፍራ ሰላማዊ ሰልፍ የማይካሄድባቸው ቦታዎች ተብለው የተጠቀሱ በመሆናቸው፣ ለተጠየቀው ሰላማዊ ሰልፍ እውቅና መስጠት አንችልም” የሚል መልስ እንደሰጠ በመግለጫው አመልክቷል፡፡

No comments:

Post a Comment